አለሕግAleHig ️
16.2K subscribers
2.84K photos
25 videos
1.86K files
3.56K links
ከጠበቃና የሕግ አማካሪ
አማራጭ የሕግ እውቀትና አገልግሎት
Alternative legal enlightenment & Service
Website: alehig.com
https://linktr.ee/alehig
WhatsApp👉 #+251920666595
Telegram👉 @MikiasMelak
የሕግ ምክርና ድጋፍ፣ የተለያዩ ህጎች፤ አዋጅ፣ ደንብ፣ መመሪያ፣ #የሕግ_መረጃ
Download Telegram
Forwarded from አለሕግ🔵AleHig
🚨#የውክልና_አሠራር_በኢትዮጵያ ⁉️ ⤵️⤵️

የኢትዮጵያ የፍትህብሄር ሕግ ቁጥር 2199 ውክልናን እንደተረጐመው “ውክልና ማለት ተወካይ የተባለ አንድ ሰው ወካይ ለተባለው ሰው እንደራሴ ሆኖ አንድ ወይም ብዙ ህጋዊ ሥራዎች በወካዩ ሥም ለማከናወን ግዴታ የሚገባበት ውል ማለት ነው” ይላል፡፡

ከትርጉሙ ለመረዳት እንደምንችለው ውክልና የሚደረገው በወካይና በተወካይ መካከል ሲሆን በውክልናው የሚከናወኑት ስራዎች ህጋዊ መሆን አንዳለባቸው ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ህጋዊ ባልሆኑ ነገሮች ላይ የሚደረግ ውክልና ተቀባይነት የለውም ማለት ነው፡፡

በሰፊው ስንመለከት ሁለት አይነት ውክልናዎችን እናገኛለን፡፡ እነሱም በፍተሃብሄር ሕግ ቁጥር 2189 ላይ የተቀመጠው ፍፁም የሆነ እንደራሴነት /disclosed or complete agency/ እና በዚሁ ሕግ ቁጥር 2197 ላይ የተቀመጠው እንደራሴው በራሱ ስም ተግባሮችን የሚፈፅምባቸው የውክልና አይነት/undisclosed agency/ ናቸው::


1. #ውክልና ለምን ያስፈልጋል? ⁉️

አንድ ሰው አንዳንድ ተግባሮችን በራሱ ከማድረግ ይልቅ ሌላን ሰው በመወከል ተግባሮቹ እንዲከናወኑለት ይፈልጋል፡፡ ለዚህም ምክንያቱ የጊዜ ጥበት፣ የቦታ ርቀት ወይም የሁኔታዎች አለመመቻቸት፣ የእውቀት ወይም የክህሎት አለመኖርና የችሎታ ማነስ ዋናዋናዎቹ ሲሆኑ ሌሎችም በምክንያትነት ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡

2. #የውክልና ምንጮች ምንድን ናቸው? ⁉️

በኢትዮጵያ ፍትሃብሄር ሕግ አንቀፅ ቁ. 2179 ውክልና ወይም እንደራሴነት አንድም ከሕግ በሌላ መልኩ ደግሞ ከውል ሊመነጭ እንደሚችል ተመልክቷል፡፡ ከሕግ የሚመነጨው ውክልና ከላይ እንደተገለፀው የውክልና ትርጉም አይነት ወካይና ተወካይ በመስማማት ስምምነት ላይ የሚደርሱበት የውክልና አይነት ሳይሆን ተወካይ የወካይን ተግባሮች ወካይ ባልፈቀደበት ሁኔታ ሊተገብረው የሚያስችለው አይነት ውክልና ነው፡፡ ይህም የውክልና ተግባር በህጉ ከተፈቀዱት የውክልና ሁኔታዎች ውጭ ሊመሠረት አይችልም፡፡ ለዚህ አይነቱ የውክልና አይነት እንደምሣሌነት የሚጠቀሱት ፤ ለአካለ መጠን ያልደረሰን ልጅ ንብረት ለማስተዳደር ሕግ የፈቀደላቸው ጠባቂዎች ውክልና አይነት እና በፍትሃብሄር ህጉ አንቀፅ ቁ. 2257 ላይ በተቀመጠው መልኩ ተግባሮችን የሚተገበሩ ሰዎች ውክልና አይነት ናቸው፡፡

ከውል የሚመነጨው ውክልና አይነት ደግሞ በፅሁፋ መጀመሪያ ውክልናን ለመተርጐም በተመለከተው መልኩ የተቀመጠው ወካይና ተወካይ የውክልና ስምምነት ውል የሚገቡበት አይነት ነው፡፡ በዚህም ፅሁፍ ውስጥ በሰፊው የሚዳሰሰው ይህ ከውል የሚመነጨው የውክልና አይነት ነው፡፡ ስለሆነም ከዚህ በመቀጠል የዚህን የውክልና አይነት አመሠራረትና የተለዩ ክፍሎቹን በፍትሃብሄር ሕግ ከቁጥር 2200-2207 በተቀመጠው መሠረት ለማየት አንሞክራለን፡፡

3 #ውክልና እንዴት ይቋቋማል? ⁉️

ውክልና በግልፅ (ማለትም ወካይ የውክልና ስልጣኑን ለተወካይ እንደሰጠው በግልፅ በማሳወቅ) ወይም በዝምታ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ተወካዩም ሊፈፅመው የሚገባው የሥራ ተግባር ስለአፈፃፀሙ በአንደንድ ህጋዊ ፎርም ውስጥ እንዲገባ የሚያስፈልገው ሲሆን ውክልናው ለተወካዩ ሊሰጠው የሚገባው ይኸው ሕግ በሚያዘው ፎርም መሠረት ነው (ፍ/ብ/ህ/ቁ.2200)፡፡ ማለትም ለምሣሌ ተወካዩ ከተወከለ በኋላ ሊያከናውናቸው የሚችሉት ጉዳዬች ወይም የሚዋዋላቸው ውሎች በፅሁፍ መሆን ግድ የሚላቸው አይነት ከሆኑ ከወዲሁ የሚደረገው የውክልና ውልም በፅሁፍ መሆን አለበት ማለት ነው፡፡

በሌላ መልኩ ውክልናውን የሚቀበለው ተወካይ መቀበሉን በግልፅ ወይም በዝምታ ሊፈጽም ይችላል፡፡ ውክልናውን መቀበል የማይፈልግ ከሆነ ደግሞ በግልፅ እንደማይቀበል በመግለፅ ከኃላፊነት እራሱን ማግለል ይችላል፡፡ ስለሆነም ተወካይ ውክልናውን የማይቀበል መሆኑን ከወዲሁ በግልፅ ካላስታወቀ በስተቀር የተወከለበት ነገር ከሚያካሂደው ሥራ ጋር ግንኙነት ያለው ጉዳይ መሆኑ በግለፅ የታወቀ ከሆነ፣ ወይም ከሙያ ሥራው አመራር ጋር የሚመሣሠል ጉዳይ ከሆነ፣ ወይም ይህንን የመሠለውን ጉዳይ ለመሥራት ፍቃደኛ ለመሆኑ በአደባባይ ገልጾ ሀሳብ በማቅረብ አስታውቆ እንደሆነ ውክልናውን እንደተቀበለ ይቆጠራል(ፍ/ብ/ህ/ቁ. 2201)።

በመሠረቱ አንድ ሰው ለቀረበለት ውል ምላሸ ሳይሰጥ ዝም ቢል የቀረበለትን የውል ሀሳብ እንደተቀበለ እንደማያስቆጥርበት የፍትሀብሄር ሕግ.ቁ 1682 ይደነግጋል፡፡ ነገርግን የውክልና ጉዳይ እንደ ልዩ ሁኔታ የሚወሠድ ስለሆነ እንድ ሰው በቀረበለት የውክልና ውል ላይ ግልፅ የሆነ ያለመቀበል ሃሣብ እስካላቀረበ ድረስ ዝምታው የውክልናውን ውል እንደተቀበለ የሚያስቆጥርበት መሆኑን የፍ/ብ/ህ//ቁ 2201 (2) ደንግጓል፡፡ ስለዚህ የውክልናው ውል ውክልናውን ባቀረበውና በተቀበለው ሰው መካከል ይመሠረታል ማለት ነው፡፡ ውክልናው የሚሰጠው ለብዙ ሰዎች ከሆነ ግን የውክልና ስልጣኑን ሁሉም ባንድነት መቀበላቸው ካልተረጋገጠ በቀር ውክልናው እንደጸና አይቆጠርም/የፍ/ብ/ህ/ቁ.2218/1/።

እንግዲህ በዚህ መልኩ ውክልናው ተቋቋመ። ውክልናው ሲቋቋም የውክልናው ወሰን እስከምን ድረስ ነው የሚለው ደግሞ በፍትሃ ብሄር ህጉ አንቀፅ ቁ 2202 ላይ ተቀምጧል። በዚህም መሠረት የውክልናው ወሰን በውሉ ላይ በግልፅ ተጠቅሶ ካልተቀመጠ በስተቀር ለውክልናው የሚሰጠው ወሰን እንደ ጉዳዩ አይነት ነው የሚሆነው (ፍ/ብ/ህ/ቁ 2202 (1))። ወካዩ የውክልናውን ወሰን በውክልናው ውል ላይ በግልፅ ካስቀመጠ ወሰኑ በግልጽ በተቀመጠው መሠረት ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ውክልናው ለአንድ ልዩ ጉዳይ ወይም ለእያንዳንዱ ጉዳዬች ወይም ለወካዩ ጉዳዮች ሁሉ ጠቅላላ ውክልና ሊሆን ይችላል (ፍ/ብ/ህ/ቁ 2202 (2))። ይህ ማለት አንድ ሰው ለአንድ ለተወሠነ ጉዳይ ብቻ ወይንም ለተለያዩ ከአንድ በላይ ለሆኑ ጉዳዬች ወይንም ለሁሉም ጉዳዬቹ ውክልና ሊሰጥ ይችላል ማለት ነው፡፡

በ ሳሙኤል ግርማ
የሕግ አማካሪና ጠበቃ
🟢 @lawsocieties
🟡 @lawsocieties
🔴 @lawsocieties
https://t.me/lawsocieties