አለሕግAleHig ️
16.2K subscribers
2.85K photos
25 videos
1.86K files
3.57K links
ከጠበቃና የሕግ አማካሪ
አማራጭ የሕግ እውቀትና አገልግሎት
Alternative legal enlightenment & Service
Website: alehig.com
https://linktr.ee/alehig
WhatsApp👉 #+251920666595
Telegram👉 @MikiasMelak
የሕግ ምክርና ድጋፍ፣ የተለያዩ ህጎች፤ አዋጅ፣ ደንብ፣ መመሪያ፣ #የሕግ_መረጃ
Download Telegram
#የአሠሪና #ሠራተኛ #አዋጅ
‘ስውር’ ማሻሻያዎች

የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁ. 377/96 በማሻሻል ሂደት ውስጥ የሙከራ ጊዜ መጠን እንዲሁም የሥራ ሰዓት ባለማክበርና በመቅረት የሥራ ውል ያለማስጠንቀቂያ ስለሚቋረጥበት ሁኔታ አከራካሪ ምናልባትም አጨቃጫቂ በመሆን ጎልተው ወጥተዋል። የገነነ የንትርክ ርዕስ ባይሆኑም የዓመት ፈቃድ እና የወሊድ ፈቃድ መጠን እንዲሁም አዲስ የተጨመሩት ወሲባዊ ትንኮሳና ጥቃት የሚመለከቱ ድንጋጌዎች በርካታ ውይይት ተደርጎባቸዋል። ሌሎች የማሻሻያ ነጥቦችም ከሠራተኛና አሠሪ ማህበራት እና ኮንፌዴሬሽን የድጋፍ ብሎም የተቃውሞ አስተያየት ቀርቦባቸዋል። የመጨረሻው ረቂቅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲቀርብ የረቂቁ ሐተታ ዘምክንያት /አጭር ማብራሪያ/ ከረቂቁ ጋር በምክር ቤቱ ድረ-ገጽ ላይ ተለቋል።
ማብራሪያው በእያንዳንዱ ማሻሻያ በተደረገበት ጉዳይ ሰፊ ገለጻ መያዝ ባይጠበቅበትም የቃላት ማስተካከያም ቢሆን እያንዳንዱን ለውጥ ምንም ሳያስቀር መዘርዝር ይኖርበታል። ‘ዋና’ በሚላቸው ላይ ብቻ ራሱን የሚገድብ ማብራሪያ የ‘ሐተታ ዘምክንያት’ ን መስፈርት አያሟላም። ‘ዋና’ ያልተባሉ ተቆርጠው የቀሩ ለውጦች በአንባቢ በዋናነት ሊፈረጁ እንደሚችሉ መረሳት የለበትም።

አዲሱ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ማሻሻያ በአዋጅ ቁ. 377/96 ላይ የተቀነሱ፤ የተጨመሩና የተለወጡ ድንጋጌዎችን ለብቻ በመለየት በሌላ ህግ ከማውጣት ይልቅ የተከተለው አቅጣጫ ነባሩን ህግ ‘ሽሮ’ እንደ አዲስ መጻፍ ነው። ሁሉም ማሻሻያዎች በአጭር ማብራሪያው ላይ ያልተዘረዘሩ በመሆኑ በተጨባጭ የተደረገውን እያንዳንዱን ለውጥ ለመለየት ነባሩንና አዲሱን አዋጅ ጎን ለጎን እያስተያዩ ማነጻጸር ይጠይቃል። አሰልቺና አድካሚ ቢሆንም በማሻሻል ሂደት ሆነ በምክር ቤቱ ውይይት ላይ ያልተነሳ ከዚህም አልፎ በማብራሪያው የተዘለለ ለውጥ መኖሩን ለማጣራት ከእንዲህ ዓይነት ንፅፅር የተሻለ አማራጭ የለም።

በንፅፅሩ አማካይነት የሚገኝ በማብራሪያው የተዘለለ ማሻሻያ እንደ ‘ስውር ማሻሻያ’ ይቆጠራል። በዚህ መልኩ ከተደረጉ ማሻሻያዎች መካከል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ።

ጡረታ እና የሥራ ጉዳት ካሣ
በአዋጅ ቁ. 377/96 ማስተካከያ ይፈልጉ ከነበሩ ኢ-ፍትሐዊ ድንጋጌዎች መካከል አንቀጽ 109/1/ በቀዳሚነት ይጠቀሳል። አንቀጹ የጡረታ ተጠቃሚነትን ከሥራ ጉዳት ካሣ ጋር አላግባብ ያቆራኛል። ሆኖም አሉታዊ ውጤቱ በሁለት ምክንያቶች ገኖ አልወጣም። የተፈጻሚነት አድማሱ መጥበብ አንደኛው ምክንያት ነው። አንቀጹ የመንግስት የልማት ድርጅት ሠራተኞችን ብቻ ይጠቅሳል። እነዚህ ሠራተኞች በሥራ ላይ እያሉ የአካል ጉዳት ሲደርስባቸው የሚያገኙት ካሣ የሚወሰነው በጡረታ ሽፋናቸው ወይም በመድን ሽፋናቸው ነው። የመድን ሽፋን ከሌላቸው ሆኖም በጡረታ ህግ ከተሸፈኑ ካሳውን በተመለከተ የጡረታ ህጉ ተፈጻሚነት ያገኛል።

ሁለተኛው ምክንያት አብዛኞቹ የመንግስት የልማት ድርጅት ሠራተኞች የመድን ሽፋን ስላላቸው የጡረታ ህጉን ተፈጻሚነት በተግባር የተገደበ አድርጎታል። ለመሆኑ የጡረታ ህጉን ኢ-ፍትሐዊ ያሰኘው ምንድነው? በዚህ ነጥብ ላይ ዝርዝር ማብራሪያው ከዚህ በፊት በለጠፍኩት ‘የአካል ጉዳት ስሌት’፤ ‘በጡረታ ያልተሸፈነና የመድን ዋስትና ያልተገባለት ሠራተኛ’ በሚለው ስር ይገኛል። በአጭሩ ለማስቀመጥ ያክል የሥራ ላይ ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ የሚከፈለው ካሳ በጡረታ ህግ ሲሰላ በንፅፅር ከአሠሪና ሠራተኛ ህጉ ስሌት በእጅጉ ማነሱ ብቻ ሳይሆን የጡረታ መብትን ያሳጣል። በሌላ አነጋገር ለጉዳት ካሳ ከተከፈለ በጡረታ ዕድሜ መድረስ ምክንያት የሚከፈለው የጡረታ አበል አይኖርም።

የጡረታ መብትን ከሥራ ጉዳት ካሳ የሚቀላቅለው የአዋጅ ቁ. 377/96 አንቀጽ 109/1/ በማሻሻያው መፍትሔ ይሰጠዋል ሲባል ጭራሽ አድማሱን አስፍቶ ሁሉንም በአዋጅ ቁ. 1156/2011 የሚገዙ ሠራተኞችን ጠቅልሎ በወሰኑ ስር ከቷቸዋል። በአሁኑ ወቅት ከሞላ ጎደል ሁሉም ሠራተኞች የጡረታ ሽፋን አላቸው። የውይይት እና የክርክር ርዕስ ያልሆነው የአንቀጽ 109/1/ ማሻሻያ ድሮ ‘የመንግስት የልማት ድርጅት ሠራተኞች’ ይል የነበረውን በማውጣት ለሁሉም ሠራተኞች ተፈጻሚ እንዲሆን አድርጎታል። ይህ ደግሞ በውጤቱ አሠሪውን በሥራ ላይ ለሚደርስ ጉዳት በአዋጅ ቁ. 1156/2011 የጉዳት ካሳ ከመክፈል ሀላፊነት ነጻ ሲያደርገው ሠራተኛውን ደግሞ ካሳውን ሲቀበል የጡረታ መብቱን ይነሳዋል።

የአዋጁ ሐተታ ዘምክንያት በአንቀጽ 109/1/ ላይ ስለተደረገው ስር-ነቀል ማሻሻያ ሳይናገር ሳይጋገር ያልፍና በቀጣዩ ንዑስ አንቀጽ ማለትም 109(2) ስለተደረገው ማሻሻያ ማብራራት ይጀምራል።

ጡረታ እና የስንብት ክፍያ
ማሻሻያው ጡረታን ከሥራ ጉዳት ካሳ ጋር እንዳቆራኘው ሁሉ ከስንብት ክፍያ ጋርም አቆራኝቶታል። በዚህ ረገድ ስለተደረገው ማሻሻያ የአዋጁ ሐተታ ዘምክንያት የስንብት ክፍያ ለማግኘት የጡረታ አበል ለመቀበል ብቁ አለመሆን እንደ ቅድመ ሁኔታ መቀመጡን ትኩረት ሰጥቶ በአጭሩ ካብራራ በኋላ ሌላውን ‘ስውር ማሻሻያ’ ግን አድበስብሶ አልፎታል። ለመጥቀስ ያክል፤

አሁን በሥራ ላይ ባለው አዋጅ በአንቀጽ 39 (1) ሥር የሥራ ስንብት ክፍያ የሚያስገኙ የቅጥር ውል ማቋረጫ ምክንያቶች ተዘርዝረው ተቀምጠዋል። ተመሳሳይ መብት የሚያስገኙ ተጨማሪ የቅጥር ውል ማቋረጫ ምክንያቶችም አዋጅ ቁጥር 494/1998 ይዞት በመጣ ማሻሻያ ተዘርዝረው ቀርበዋል። ረቂቁ ሌሎቹን አዋጆች የሚሽር ስለሆነ እነዚህ ተበታትነው የነበሩት ዝርዝሮች ለተደራሽነት ሲባል ወደ አንድ ሰነድ ማጠቃለል ስለሚገባው ይህንኑ ሥራ ተከናውኗል። አንዳንዶቹ የቅጥር ውል ማቋረጫ ምክንያቶችም ላይ ማስተካከያ ተደርጓል። (ሰረዝ የተጨመረ)

እንዲሁ እንደዋዛ ‘ማስተካከያ ተደርጓል’ በሚል ተድበስብሶ የታለፈው ማሻሻያ በይዘቱ ነባር መብትን ከህጉ የፋቀ መሰረታዊ ማሻሻያ ነው። በአዋጅ ቁ. 494/1998 በጡረታ መገለል (የጡረታ ዕድሚ በመድረሱ) ለስንብት ክፍያ ከሚያበቁ ምክንያቶች አንዱ ሆኖ ተጠቅሷል። ሆኖም መብቱ የሚሰራው የፕሮቪደንት ፈንድ ሽፋን ወይም የጡረታ ለሌለው ሠራተኛ ብቻ ነው። በማሻሻያው ይህ ተቆርጦ ወጥቷል። በማሻሻያው የተነሳ የፕሮቪደንት ፈንድ ሽፋን ሆነ የጡረታ መብት የሌለው ሠራተኛ በጡረታ ሲገለል የስንብት ክፍያ የማግኘት መብት ያጣል። እንዲህ ዓይነት ግዙፍ የመብት ማሳጣት ውጤት ያለውን ማሻሻያ ሐተታ ዘምክንያቱ ‘ማስተካከያ’ በሚል አድበስብሶ ያለፈው ለምን ይሆን?

የመብት እና ግዴታዎች መታገድን ተከትሎ የውሉ መቋረጥ
ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎች መታገድን በሚገዛው የህጉ ክፍል /አንቀጽ 17-22/ ላይ መጠነኛ እና መሰረታዊ የሚባሉ በድምሩ አራት ማሻሻያዎች የተደረጉ ቢሆንም ሀተታ ዘምክንያቱ አንደኛውን ብቻ በመምዘዝ በአንድ ዓረፍተ ነገር ለማብራራት ሞክሯል። ሰነዱ በአንቀጽ 22 ላይ የተደረገውን ማሻሻያ ይጠቅሳል፤ ‘አሠሪውም ለሥራ የሚቀርበውን ሠራተኛ ወደ ሥራ መመለስ አለበት’ ይል የነበረው ተቀይሮ ‘አሠሪውም ለሥራ የሚቀርበውን ሠራተኛ ከሙያው ጋር አግባብነት ባለው የሥራ መደብ ላይ ቀድሞ ሲከፈለው የነበረውን ደመወዙን በመጠበቅ ወደ ሥራው መመለስ አለበት።’ በሚል ተሻሽሏል።